ዋዜማ ራዲዮ- የኳታር ወታደሮች ከአወዛጋቢው የጅቡቲና የኤርትራ ድንበር ለቀው መውጣታቸውን ተከትሎ ኤርትራ አወዛጋቢውን የራስ ዱሜራ ኮረብታ ወራ መያዟ ተሰምቷል።
ኤርትራ ወረራ ስለመፈፀሟ ማስተባበያ አልሰጠችም፣ ይልቁንም በኳታር ድንገተኛ ለቆ መውጣት ግራ መጋባቷን ገልፃለች። ጅቡቲ በበኩሏ የኣአፍሪቃ ህብረት በጉዳዩ ጣልቃ እንዲገባ ተማፅናለች።
በአካባቢው የተፈጠረውን ቀውስ ተከትሎ የኢትዮዽያ መንግስት ጉዳዩን በልዩ ሁኔታ ሲከታተለው እንደነበረ ለመንግስት ቅርብ የሆኑ ምንጮች ይናገራሉ።
የኤርትራ መንግስት አዲስ እርምጃ ያሳሰባት ኢትዮዽያ በጉዳዩ ላይ አስቸኳይ ምክክር በማድረግ ጉዳዩን የሚከታተል የደህንነት የመስክ ቡድንና የመንግስትን ቀጣይ እርምጃ የሚመራ ኮማንድ ፖስት ለማቋቋም ሀሳብ ቀርቧል።
የኢትዮዽያ የፀጥታና የደህንነት ምክር ቤት የተወስኑ አባላት ባደረጉት ውይይት በቀጣዩ ሳምንት ሲቪልና ወታደራዊ አካላትን ያካተተ ምክክር ለማድረግ መታቀዱን የዋዜማ ምንጮች ነግረውናል።
“በጅቡቲ ላይ የሚፈፀም ወረራ የኢትዮዽያን የወደብ አገልግሎት አደጋ ላይ እንዳይጥል ከዚህ ቀደም የተቀመጠ አቅጣጫ ስላለ አዲስ እርምጃ ይኖራል ብዬ አልገምትም” ይላሉ ከጉዳዩ ጋር ቅርበት ያላቸው የፀጥታ አማካሪ።
ኢትዮዽያ የወደብ አገልግሎቷን ለመከላከል ወታደር እስከመላክ ድረስ ዝግጁ መሆኗን ግን ደግሞ በጅቡቲ በርካታ የውጪ ሀይላት በመኖራቸው የአስመራ መንግስት ከድንበር አካባቢ አልፎ ጅቡቲ ላይ ወረራ የመፈፀም አቅምም ፍላጎትም ሊኖረው አይችልም ብለው እንደሚያምኑ አማካሪው ይናገራሉ።
በጅቡቲ የባህር መስመርን ደህንነት ለመጠበቅ በመቶዎች የሚቆጠሩ ወታደሮችን የያዘ ልዩ ተወርዋሪ ሀይል ከዓመታት በፊት ተቋቁሞ እንደነበር ይታወሳል።
የኢትዮዽያ መንግስት በኤርትራ ላይ አዲስ የፀጥታ ፖሊሲ ስነድ አዘጋጅቶ የጨረሰ ቢሆንም መወሰድ ባለበት እርምጃ ላይ ከስምምነት ባለመደረሱ እንዲሁም ወደ ጦርነት የሚወስድ አማራጭ ላይ በተፈጠረ ሙግት ፖሊሲው በእንጥልጥል ተይዟል።
The post ኢትዮዽያ ኤርትራ በጅቡቲ ላይ የፈፀመችውን ወረራ የሚከታተል ኮማንድ ልታቋቁም ነው appeared first on ሳተናው: Ethiopian Amharic News | Breaking News: Your right to know!.