በ ፋኑኤል ክንፉ / ሰንደቅ
ብአዴን-ኢሕአዴግ በዓመት ሁለት ጊዜ “አብዮታዊ ዴሞክራሲ” የሚል ስያሜ ያለው የድርጅቱ ልሳን መጽሔትን ያሳትማል። በዚህ ወር ለንባብ የበቃው የድርጅቱ ልሳን መጽሔት፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ማሕበራዊና ድርጅታዊ ጉዳዮችን እና ተሞክሮዎችን በስፋት የዳሰሰ ነው። የዚህ የጥር ወር 2009 ዓ.ም. የታተመውን አብዮታዊ ዴሞክራሲ መጽሔት በወፍ በረር ለመቃኘት ተሞክሯል።
እንደሚታወቀው ኢሕአዴግ “ጥልቅ ተሃድሶ” የሚል ስያሜ የሰጠውን ተሃድሶ በፓርቲ እና በመንግስት መዋቅር ውስጥ አካሂዶ ጨርሷል። ብአዴን- ኢሕአዴግም ከተሃድሶ ንቅናቄው ጋር የተያያዘ ጥናታዊ ጽሁፍ አዘጋጅቶ ለአባላቱ እና ለባለድርሻ አካላት አትሞ አሰራጭቷል። የድርጅቱ ልሳን መጽሔት ተላላፊ እና ገዳይ የፖለቲካ በሽታዎች ሲል አምስት ፍሬ ነገሮች አስቀምጧል።
በዚህ ዓመት በአማራ ክልል የተፈጠረው የፖለቲካ የማሕበራዊ ቀውስ መሰረታዊ መነሻዎች ናቸው ያላቸውን በግምገማ የተገኙ ነጥቦች ከማስቀመጡ በላይ፣ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ የተሃድሶ መሰረታዊ አስተሳሰቦች እና አካሄዶችን ያሳያሉ ያላቸውን የሀገሮች ተሞክሮ በዝርዝር ለማስቀመጥ ብዙ ርቀት ሄደዋል። ለአብነት ከቀረቡት መካከል፣ የፈረንሳይ ሶሻሊስት ፓርቲ፣ የጀርመን ሶሻል ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ የሲንጋፑር ፒፕልስ አክሽን ፓርቲ፣ የሕንድ ናሽናል ኮንግረስ ፓርቲ እና የደቡብ አፍሪካ ናሽናል ኮንግረስ ፓርቲ ናቸው። የተጠቀሱ ሀገሮች ከብአዴን-ኢሕአዴግ ርዕዮተዓለም ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ወይም ሙሉ ለሙሉ መመሳሰል ያላቸው ሳይሆኑ፣ ካስቀመጡት መስመር አንፃር የደረሰባቸውን የፖለቲካና የማሕበራዊ ቀውሶች እንዴት መወጣት እንደቻሉ ተሞክሮ ለመውሰድ ያለመ መሆኑ በግልፅ ሰፍሯል።
ድርጅቱ በተሃድሶ ነቅሶ ያወጣቸው ተላላፊና ገዳይ የፖለቲካ በሽታዎች ያላቸው ሲደመሩ የሚያሳዩት ውጤት፣ የድርጅቱ ማሕበራዊ መሰረቶች የሆኑትን የህብረተሰብ ክፍል አስቀይመዋል። ከዚህም በላይ ርቀው በመሄድ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶቻቸውን የማያከብሩ ፀረ-ዴሞክራሲያዊ አያያዞች መስተዋላቸውን ሰነዱ አስቀምጧል።
ድርጅቱ በተሃድሶ ነቅሶ ያወጣቸው ተላላፊና ገዳይ የፖለቲካ በሽታዎች ያላቸው በተለይ ከአማራ ክልላዊ መንግስት እና አስተዳደር አንፃር ስንመለከተው፤ የአማራ ሕዝብ ቢከፋው፣ ቢያምፅ፣ ተቃውሞውን ቢያሰማ ተገቢነቱ ከፍ ያለ ነው። የአማራ ሕዝብ ቅሬታዎች ቅቡል መሆናቸውን በተጨባጭ የሚያሳይ ነው። በአንፃሩ ይህንን የአማራ ሕዝብ ችግሮች መነሻ በማድረግ ማሕበራዊ መሰረት ሳይፈጥሩ፣ የሕዝቡን ችግሮች ለራሳቸው ፍላጎት መጠቀሚያ ለማዋል የተንቀሳቀሱ ኃይሎች ትዝብት ውስጥ ከመውደቅ ውጪ ያተረፉት አንዳች ነገር የለም። በተለይ በአማራ ሕዝብ እና በትግራይ ሕዝቦች መካከል ለዘመናት የነበረውን የማሕበራዊ የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ትስስሮሽን ለመበጣጠስ እና በሕዝቦቹ መካከል የበቀለኝነት የደም መስመር ለማስመር ሲሯሯጡ ለነበሩ ኃይሎች የኢትዮጵያ አምላክ ይፋረዳቸው።
እንዲሁም ድርጅቱ የዘረዘራቸው ተላላፊና ገዳይ የፖለቲካ በሽታዎች ያላቸው በፍጥነት ሊያክማቸው ካልቻለ በአማራ ክልል የማሕበራዊ አብዮት እንቅስቃሴዎች መከሰታቸው አይቀሬ ነው። በርግጥ በሰነዱ ላይ እንደሰፈረው፣ “ተግባርን የመሰለ ፍትሃዊ ዳኛ የለምና፣ የመታደስ ጉዳይ የአንድ ሰሞን ሁከትና ግርግር ሳይሆን በቀጣይነት የጠራ መስመር የመጨበጥና በተግባር የመተርጎም ጉዳይ ነው” ይላል። ሁላችንም የምናየው ነው የሚሆነው።
በዚህ አምድ ብአዴን/ኢህአዴግ በጥልቅ ተሃድሶ አምስት ተላላፊና ገዳይ ፖለቲካዊ በሽታዎች ከነመንስኤዎቻቸው ደርሼባቸዋለሁ ያለውን አቅርበነዋል። አንባቢዎቻችን የራሳችሁን ግንዛቤ ውሰዱ።
የርዕዮተ ዓለማዊና ፖለቲካዊ አስተሳሰብ
መሸርሸርና ከመሰረታዊ መስመሮች መውጣት
የኪራይ ሰብሳቢነትን የፖለቲካ ኢኮኖሚ በመናድ የልማታዊ የፖለቲካ ኢኮኖሚን የመገንባት አስተሳሰብን ቀርፆ፣ በተግባር ለውጥ ለማምጣት የተሰማራው አመራር የድርጅቱን መስመር ከጥቀት መጠበቅ ተስኖት ታይቷል። አስተሳሰብ ግንባታን ማዕከል ያደረገ የመስመር ማጥለቅ ስራ በብዛት አልተሰራም፤ ይልቁንም በቴክኒካል ስራዎች አፈፃፀም ላይ መታጠር ታይቶበታል። አመራሩ እራሱን በንባብና በተግባር እያስተማረና እያበቃ በተቋሙ ውስጥ ልማታዊ ዴሞክራሲዊ መስመሩ ይበልጥ እንዲሰርጽ በማድረግ በኩል የትኩረት ማነስና ስንፍና እንደተስተዋለበት ታይቷል።
በግምገማ እንደተረጋገጠው፣ የመስመር ግልጽነት መጓደል፣ የያዘውን የመልቀቅና የህዝባዊ ውግንና መሸርሸር ታይቶበታል። “አውቃለሁ” እያለ መስመሩን ከላይ ከላይ ቢገልጽም፣ በጥልቀት ሳይጨብጠው እንደቆየ ግልጽ ሆኗል። “መስመሩን ይዣለሁ” የሚለውም በጥልቀት ጨብጦ መስዋዕትነት ሊከፍልበት መዘጋጀቱን የሚያረጋግጥ ተግባራት የማከናወን ድክመት ታይቶበታል። መስመሩ በቀጣይነት በማህበራዊ መሰረቱ ላይ እንዲሰርፅም አጥጋቢ ስራ ሳይሰራ ቆይቷል።
የአብዛኛው ህዝብ መድህን የሆነውንመስመር አንግቦ ከመፋለም ይልቅ፣ በኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰቦች መዋጥ ተስተውሎበታል። ጎራ ከመደበላለቅ አልፎ ቀላል ባሆነ ደረጃ የጠላት አስተሳሰቦችና አቋሞች ሲራመዱ ታይተዋል። ከልማታዊ ዴሞክራሲያዊ መስመር የራቁ የትምህርት አስተሳሰቦችና ተግባራት በግላጭ ሲታዩ፣ በሁኔታው ተውጧል፣ ኋላቀር አስተሳሰብን መዋጋትም ብርቅ እንደነበር ግልጽ ሆኗል። አርሶ አደሩንና ሌሎች የልማታዊ ዴሞክራሲያዊ ማህበራዊ መሰረቶቹን እየዘነጋ፣ ከማህበራዊ መሰረቶቹ ውጪ ለጥገኛ ባለሀብቶች የሚያጋድል አመራር የመሆን አዝማሚያ ታይቶበታል።
የአባላትን ምልመላና ግንባታ እንዲሁም የድርጅቱን ፕሮግራምና መተዳደሪያ ደንብ ማዕከል አድርጎ፣ በዚሁ ተዋረድ የተገነቡ መመሪያዎችንና አሰራሮችን በጥብቅ ዲስፕሊን ይዞ የግንባታ ሥራውን የማካሄድ ጉድለት ታይቶበታል። ድርጅት የሰዎች ስብስብ ነው። ጠንካራ ታጋዮች የተሰባሰቡበት ከሆነ ጥሩ ድርጅት ይሆናል። በአመራር ምልመላና ስምሪት ወቅት በቂ እውቀት ይዞ በተግባር የተፈተኑትን እየለዩ ግልጽነት ባለው አሰራር ወደ አመራር በማምጣት እንዲሁም በሂደት የሚስተዋሉ ዝንባሌዎችን እየለዩ በመገንባት በኩል በጥብቅ ክትትል የመምራት ጉድለት ነበር። ይህም በመሆኑ በየደረጃውና በየተቋማቱ የተሻለ አቅም ያላቸውና ህዝባዊ አመራር በመስጠት ሊያረጋግጡ የሚችሉ ሰዎች ወደ ድርጅቱ በሚፈለገው ደረጃ ተመልምለው አልገቡም።
አመራሩ ጠንካራ የአስተሳሰብና የተግባር አንድነት እየገነባና ሁኔታዎችን በጥልቀት እየገመገመ፣ የአመራር ሚናውን ማረጋገጥ ሲገባው፣ ከዚህ አካሄድ ያፈነገጡ ሁኔታዎችን በጥልቀት እየተጋለጠና ችግሮችን ወደ ውስጥ እየተመለከተ ከመሄድ አኳያ ችግሮች ታይተዋል። ወቅታዊ ፖለቲካዊ ሁኔታውን በጥልቀት አለመረዳትና የሚያስከትሉትን አደጋ በብቃት አለመመዘንም ተገምግሞ ትምህርት ተወስዶበታል። እንዲሁም በተጨባጭ ግምገማና በዝንባሌ ትንተና ላይ ያልተመሰረተ፣ ጥብቅ የአመራርና የስራ ዲስፕሊን መጓደል፣ የትግልና የለውጥ አብነት አለመሆን እንዲሁም፣ የርዕዮተ አለማዊና ፖለቲካዊ አስተሳሰቡ ደካማ መሆኑ ተረጋግጧል።
የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብንና ተግባርን
በቀጣይነት ያለመታገል ሁኔታ
የክልላችንም ሆነ የአገራችን የፖለቲካ ኢኮኖሚ ልማታዊ ሳይሆን ኪራይ ሰብሳቢነት ወይንም ህገወጥ ተጠቃሚነት ሰፍኖበት የቆየ ነው። ይህንን የፖለቲካ ኢኮኖሚ በልማታዊ ዴሞክራሲያዊ የፖለቲካ ኢኮኖሚ መለወጥየግድ ይላል። አመራሩ የችግሩን ስፋትና ጥልቀት ግምት ያስገባ የለውጥ ንቅናቄ በማካሄድ በኩል የአስተሰብና የአፈፃፀም ችግሮች ታይተውበታል። የአስተሳሰብ ችግሮችን በሚመለከት በርካታ መገለጫዎች በአመራሩ ዘንድ በስፋት ተስተውለዋል። በተግባርም ኪራይ ሰብሳቢነትን የሚደፍቁ፣ ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ ተግባራትን የሚያሳድጉ ተግባራትንም በማከናወን ረገድ መሰረታዊ ድክመቶች እንደተስተዋሉበት በግምገማ ተረጋግጧል።
የሙስናን ተግባራት በተመለከተ በየደረጃውና በሚመራው ተቋም፣ የባለሀብቶችንና የአመራሩን መርህ አልባ ጉድኝቶች አነፍንፎ፣ የስርዓቱን ጤንነት ለመጠበቅ የማይተጋ፣ ሰምቶ እንዳልሰማ የሚያልፍና የማይታገል አመራር ሆኖ መሰንበቱም ታይቷል። በኢንቨስትመንት ስም ሰፋፊ መሬቶችን አጥረው፣ አንድም ልማት የማያለሙ ብቻ ሳይሆን፣ ለሌሎች አልሚዎች እንቅፋት ሲሆኑ አይቶ እንዳላየ የሚያልፍ፣ የማይታገልና ርምጃም የማይወሰድ ነበር፣ ከዚህም የተነሳ ለተለያዩ ጥርጣሬዎች ተጋልጦ ቆይቷል።
ከመሬታቸው ለሚነሱ አርሶ አደሮች ካሳ አከፋፈል በወቅቱ በመክፈልና በተገቢ መንገድ በማቋቋም ረገድ ድክመቶች ታይተዋል። በግብር አሰባሰብ፣ በግንባታ ኮንትራት አስተዳደር፣ ፍትሃዊ የንግድ ስርዓት በአግባቡና በንጽህና እንዲፈፀም አመራር በመስጠት ረገድም ድክመቶች ታይተውበታል። በኮንስትራክሽን፣ በግዥ፣ በሰው ኃይል ስምሪት፣ ወዘተ የሚደርሱትን ጥቆማዎችና የሚሰማቸውን ብልሹ አሰራሮች በማስተካከል በኩል ጉድለቶች ነበሩበት። የያዘውን የህዝብ ኃላፊነት የህዝብ ኑሮ መለወጫ ማድረጉ ቀርቶ፣ የመንግስት ስልጣን አተያዩና አጠቃቀሙ የተዛባ እንደነበርም ታይቷል። ስልጣንን የኑሮና የሀብት መሰረት አድርጎ የመመልከት አዝማሚያ ታይቶበታል። ተጠያቂነት የሰፈነበት የስራ አፈፃፀምን ማሳደግም ላይ ችግሮች ነበሩ። ስለሆነም ውጤታማ ሳይሆኑ በመንግስት ስልጣን የመቆየት ዝንባሌ አንዱ መስተካከል ያለበት ጉዳይ እንደሆነ ተገምግሟል።
የህዝብን አንገብጋቢ ችግሮች ለይቶ በመፍታት ረገድ
የታዩ ድክመቶች
አመራሩ ዝንባሌዎችን እየተነተነ፣ ፖለቲካዊ አንድምታቸውን እየተገነዘበ፣ ችግሮች ከፍተኛ ደረጃ ላይ ሳይደርሱ ህዝብን እያሳተፈ የመፍታት መሰረታዊ ጉድለቶች ነበሩበት። በችግሮቹ አፈታት ዙሪያ ጥበብ የማነስም፣ የአተያይ ጉድለትም አጋጥሞታል። የአመራር ሂደቱም ዳተኛ እንደሆነ ተገምግሟል። ህዝብ የሚያነሳቸውን ጥያቄዎች፣ እንዲሁም በየተቋማቱ የሚነሱ ችግሮችንና አለመግባባቶችን ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ፈትቶ ውጤታማ በመሆን በኩልም ችግሮች እንዳሉ ተለይቷል።
በግብርና ምርታማነት እድገት የመጣ ቢሆንም፣ ማደግ በሚገባው ደረጃ አላደገም። ይህም የገጠሩ ህዝብ በሚፈልገው ደረጃ እንዳይሻሻል እንቅፋት ሆኗል። በመሆኑም አመራሩ መሰረታዊ ለውጥ አላመጣም። በተለይም የግብርና ምርታማነት ስነምህዳርን ያማከሉ የምርምር ውጤቶችን በማውጣትና የአርሶ አደሩን የቴክኖሎጂ አጠቃቀም በሚፈለገው ደረጃ እንዲሻሻል በማድረግ በኩል የተሰራው ስራ ብዙ ችግሮች ያሉበት መሆኑ ተገምግሟል። በከተሞቻችንም የአምራች ኢንዱስትሪ መስኮችና የንግድ ስራ እንቅስቃሴ ምርታማነት እድገት በሚፈለገው ደረጃ እንዳላደገና ቀጣይ ርብርብ እንደሚጠይቅ ግልፅ ሆኗል።
የከተማውን ህብረተሰብና በገጠርም ቢሆን ቁጥሩ ጥቂት የማይባል ህብረተሰብ፣ መሰረታዊ የምግብ ፍጆታዎችን የሚሸምት በመሆኑ፣ ከምርታማነት አለማደግ፣ ከገቢ ምንጮች አለመስፋፋትና አለማደግ ጋር የተያያዘ የኑሮ ውድነት እያሰቃየው ይገኛል። እነዚህንና ተጓዳኝ ችግሮችን በብቃት በመፍታትና በለውጡ ላይ የተመሰረተ ተስፋ እያሳደጉ አመራርን በማረጋገጥ ረገድ ብዙ ችግሮች እንደነበሩ ግምገማው አረጋግጧል።
ስራ አጥነት በገጠርና በከተሞች እየተስፋፋ መሄዱ ግልጽ ነው። በጥቂቱ የሚገኘው የስራ እድልም በዘመድ፣ በአድሎና በትስስር የሚያዝ በመሆኑ፣ ወጣቱን ተስፋ እያስቆረጠ እንደሄደና ችግሩን የሚፈታ ጥረት መካሄድ እንዳለበት ታይቷል። የጥቃቅንና አነስተኛ አንቀሳቃሾች ተጨባጭ ሁኔታ፣ የወጣቱን ተስፋ የሚያለመልሙ መሆናቸው እየቀረና የወጣቶቹ መደራጀት እንደ መጨረሻ ግብ እየተቆረጠ መሄዱ፣ የወጣቱን ሰርቶ የመለወጥ ፍላጎት ተፈታትኖታል። አመራሩ በየሚመራው ተቋም ያለውን የስራ እድል ወጣቱን ተሳታፊ በማድረግ ትኩረት ሰጥቶ አለመስራት፣ ቅንጅታዊ አሰራር መጓደል፣ ግብአትን (ብድርን) በቀልጣፋ አሰራር አለማቅረብ፣ ይልቁንም በመመሪያ ማጠርና ባለው የመልማት እድል ልክ አቅዶ ተግባራዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ረገድ፣ ከፍተኛ ችግሮች በመታየታቸው የተነሳ፣ እነዚህን ችግሮች የሚፈታ ርብርብ መካሄድ ይኖርበታል።
የወጣቶችና የሴቶች አደረጃጀቶች በጥቅሞቻቸው ዙሪያ ተሰልፈው እንዲታገሉ የሚያደርግ ችግር ፈቺ ድጋፍ አለማድረግ፣ ሴቶች ከሚደርስባቸው ተፅዕኖ እንዲሁም ኋላቀር አስተሳሰብና ተግባር እንዲላቀቁ በሚያደርግ አግባብ ስራውን አለመምራት፣ አደረጃጀቶችንም መሬት አስነክቶ ተግባራዊ እንቅስቃሴ በማድረግ በኩል መሰረታዊ ችግሮች ተገምግመዋል። የልማት ማዕከላትን (Growth Corridor) የተከተለ ልማትና ድጋፍ አለመስጠት፣ በዝናብ አጠርና በደጋማ አካባቢዎች ለሚኖረው ህዝብ በቂ ቴክኖሎጂዎችና የተሻሻሉ አሰራሮች ቀርበው ህይወቱን የሚለወጡ ተግባራት በአጥጋቢ ሁኔታ አልተካሄዱም፣ ስለሆነም እነዚህን የሚለውጥ ርብርብም ጠይቋል።
ከወሰንና ከማንነት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን በህዝባዊነት መንፈስ ተመልክቶ፣ በወቅቱና በትክክለኛው አግባብ የመፍታቱ ሥራ ጊዜ ወስዷል። የችግሮችን ባህሪና ፖለቲካዊ አንድምታቸውን ተረድቶ እንዲሁም የችግሩን ምክንያቶች ወደ ውስጥ ተመልክቶ መፍትሄ ከመስጠት ይልቅ የስሜት መጫጫንና፣ ውጫዊ ማድረግ የታየበት ወቅት ነበር። ህዝብን የሚያረጋጋ ስራ በመስራት በኩልም ችግሮች የተስተዋሉበት ነበር። ከዚህ በመነሳትም በህዝቦች ዘንድ ቅሬታና አለመግባባት እንዲፈጠር ምክንያት ሆኗል።
የክልሉንና የየአካባቢዎችን እቅድ በማዘጋጀት፣ በእቅዱ መሰረትም ፈጻሚን በማብቃትና ውጤታማ የክትትልና ድጋፍ ስርዓት በመዘርጋት የአመራርነት ሚናን የማረጋገጥ መሰረታዊ ድክመቶችም ታይተዋል። በየአካባቢው ያለውን የልማት አቅም ተጠቅሞ፣ የህዝቡን ኑሮ ለመለወጥ ከመረባረብ ይልቅ “አልተጠቀምንም” በሚል አንጋጦ ማየት ተስተውሏል። በገጠርና በከተሞች ህዝብን የሚያስመርሩ የመልካም አስተዳደር በደሎች ላይ ስር ነቀል ለውጥ ያለማምጣት ችግሮች ተገምግመዋል። በተለይም የሴቶችን የመልካም አስተዳደር ችግሮች የመፍታት፣ ቅንጅታዊ አሰራሩን አዳብሮ የመንቀሳቀስና እልባት እንዲያገኙ የማድረግ ድክመቶች ሲታዩ ቆይተዋል።
በፌዴራልም ሆነ በክልል የሚሰሩ የመሰረተ ልማት አውታሮች ግንባታ በጥራትና በወቅቱ እንዲከናወኑ መርህ ላይ ቆሞ በመታገልና በማስተካከል ረገድ ድክመቶች ነበሩ። በክልሉ አንዳንድ አካባቢዎች የተጀመሩ የመንገድ፣ የውሃ፣ የመስኖና የቤቶች ልማት ግንባታዎች ተጓትተዋል፣ ጥራት የጎደላቸው መሆናቸውም ተገምግሟል። ችግሮቹንም በወቅቱ ክትትል አድርጎ መፍትሄ በመስጠት በኩል የቁርጠኝነት ችግሮች ነበሩበት። የሲቪል ሰርቪስ፣ የፍትህ፣ የፋይናንስ፣ የአመራርና ሌሎች የማሻሻያ ፕሮግራሞች በውጥን ታቅደውና ተጀምረው የቀሩበት ሁኔታም እንደነበር ተገምግሟል። ተግባራቱን በጥብቅ ይዞ ውጤት በሚያመጣ አግባብ የመምራት ጉድለት ነበር። የተበላሹ አለሰራሮችንና የስራ ድክመቶችን ፈልፍሎ አውጥቶ ተጠያቂ የሚያደርግ፣ የተበላሹትን የሚያርምና የጠነከሩትን የሚያበረታታ ጥበቅ አሰራር ተነድፎ የህዝቡን ችግሮች በሚፈታ መልኩ ስራ ላይ እንዲውል የአመራርነት ሚናውን አላረጋገጠም።
አድርባይነትና ፀረ-ዴሞክራሲ በድርጅቱ ውስጥ ገንግኗል
ድርጅቱ ዴሞክራሲዊ ባህሪው እያደገ፣ የታጋዮችና የተራማጆች ድርጅት መሆን ሲገባው፣ በሂደቱ ከዚህ በተቃራኒው ፀረ-ዴሞክራሲና አድርባይነት እየተስፋፋ እንደመጡ ተረጋግጧል። በውስጠ ድርጅት ዴሞክራሲው፣ ለየት ያለ ሃሳብ በሚቀርብበት ሁኔታ በብቃት ለመደማመጥ የዝግጁነት ችግር ታይቷል። በየደረጃው የሚነገረውን መስማት እንጂ ያለ ማዳመጥ ሁኔታም ነበር። “አዳምጫለሁ” ቢልም በተግባር ያለመተርጎም ሁኔታ ነበር። አዳምጦ ይተወዋል፣ የተስማማ መስሎ አለመስማማቱን በተግባር የመግለፅ አዝማሚያዎችም ነበሩ። የማዳመጥ ችግሩ በአመራሩ መካከል ብቻ ተወስኖ የቀረ ሳይሆን፤ ወደ ሁሉም አቅጣጫዎች ተስፋፍቶ ዘልቋል። በዚህም የተነሳ፣ ከድርጅቱ አመራሮችና አባላት አልፎ እስከ ህዝቡ ድረስ ዘልቆ “ትሰማላችሁ እንጂ አታዳምጡም፤ ብታዳምጡም ወደ ተግባር አትቀይሩም!” እስከማለት ደርሷል።
በየደረጃው ማለትም በከፍተኛ፣ በመካከለኛ፣ በጀማሪና በታችኛው አመራር መካከል ዴሞክራሲያዊ ግንኙነቱ መሆን በሚገባው ደረጃ ላይ ያልደረሰ፣ አልፎ ተርፎም አድርባይነትና ፀረ-ዴሞክራሲ፣ መጠቃቃትና አድሮ መኖር የተጣባው እንደነበር በግምገማው ግልጽ ሆኗል። መርህ ላይ ቆሞ ሁሉም ለዴሞክራሲና መርህ ላለው ግንኙነት መታገል ሲገባው፣ መርህ አልባነት ተስተውሏል። ወጥነት ባለው መስመር ላይ የተገነባ የአመራርነት ሚናውን የማረጋገጥ ጉደለቶች ነበሩ። በአመራሩና በህዝቡ መካከል መገንባት የነበረበት መርህ ያለው ግንኙነትም፣ መርህ የጎደለውና ለቀጣይ እድገትና ለውጥ አቅም የማይፈጥር አቅጣጫን ይዞ ሰንብቷል። የምንሰራውን እንደምንሰራ፣ የማንሰራውን ጊዜ እንደምንፈልግ በግልጽ ተናግሮ ከመታገል ይልቅ፣ የማይፈፀም ቃል መግባት ተስተውሏል። አልፎ አልፎም ከመደበኛው አሰራር ውጭ ከአመራሩ ይልቅ በሽማግሌዎችና በጉዳይ አስፈፃሚዎች አቤቱታ ላይ ተመስርቶ ውሳኔ መስጠት ትክክለኛ ያልሆነ የችግር አፈታት ስርዓት እንዲስፋፋ የራሱን አስተዋጽኦ አበርክቷል።
የብዙሃንና የሙያ ማኅበራት፣ ልዩ ልዩ የህዝብ አደረጃጀቶች ነፃነታቸውን ጠብቀው የህዝብ መታገያ ተቋማት በሚሆኑበት ደረጃ ድጋፍ እንዳልተካሄደ ተረጋግጧል። ማኅበራዊ መሰረቶቻችንን ከሚያስቀይሙና በበጎ ተጽዕኖ ከሚፈፀሙ ተግባራት በላይ፣ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶችን የማያከብሩ ፀረ-ዴሞክራሲ አያያዞችም ተስተውለዋል። ይህንንም በአግባቡ የሚያርም ስራ ሳይሰራ ቆይቷል። የመንግስት አሰራር ተጥሶ በሕገ-ወጥነት ስራዎች ሲሰሩ አልታገለም፤ አይቶ እንዳላየ ያልፋል፤ ለምሳሌ ሕገ-ወጥ የቤቶች ግንባታዎች፣ እንዲሁም ሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር በአካባቢው ሲታዩ ታግሎ የማስተካከል ችግሮች ታይተዋል። በየወቅቱ የሚታዩትን ችግሮች በመተራረምና በመገንባት መንፈስ ከማየት ይልቅ፣ የመጠቃቃትና ፀረ-ዴሞክራሲ የሆነ እንቅስቃሴ መካሄድም አልፎ አልፎ መታየት ጀምሯል።
ትክክለኛና ወቅታዊ ሁኔታዎችን በትክክለኛ ሃሳብ ከመግለፅ ይልቅ፣ ያልተገባ ድጋፍ መፈለግ እንደነበር ተገምግሟል። ለማኅበራዊ ህይወቱ የማድላት ሁኔታም የታየ ጉዳይ ነው። አልፎ አልፎ በሂስና በሂስ መልሶች በፀረ-ዴሞክራሲና በሚያሸማቅቅ ሁኔታ ገልብጦ የመገምገም ዝንባሌዎች የፀረ-ዴሞክራሲ መገለጫዎች ነበሩ።
በዘረኝነት የማገለፅ ፀረ-ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብና ተግባርም ሌላው መገለጫ ነው። ብዝሃነት በሰፈነባት ክልላችንና አገራችን በማንነት ላይ ተመስርቶ ማቅረብና ማራቅ ፍፁም ፀረ-ዴሞክራሲ ከመሆኑም በላይ፣ ለህዝቦች አንድነት እንቅፋት ነው። በየደረጃው የሚገኙ አመራሮችና አባላት ቀላል ባልሆነ ደረጃ ለዚህ ዓይነት መጥፎ በሽታ ተጋልጠው መገኘታቸው ምን ያህል አደገኛ እንደሆነ ታይቷል።
የትምክህት አስተሳሰብና ተግባር
ከመቼውም ጊዜ በላይ ገኖ የተስተዋለበት ወቅት
በተከታታይ በተካሄዱ የትግል መድረኮች፣ አንድ ወቅት ወደ ዳር ተገፍቶ የነበረው ትምክህት፣ ትግሉ መቀዛቀዝ ባሳየበት ወቅት ህዝብን ከህዝብ የሚያፋጅ የመድረኩ ቀንደኛ ጠላት ሆኖና ገኖ የታየበት ሁኔታ ነው የነበረው። አመራሩ በየወቅቱ በውስጡም ሆነ በኅብረተሰቡ መካከል የሚታዩ ችግሮችን እየታገለ ባለመሄዱ፤ የትምክህት አስተሳሰቡ እየሰረፀው ሂዶ የተዛባ አስተሳሰብና ተግባር ውስጥ ወድቆ ሰንብቷል።
በአማራ ጠገዴና በትግራይ ፀገዴ ወረዳዎች መካከል የተነሳውን የወሰን ማካለል ጥያቄ፣ በአግባቡና በወቅቱ ለመፍታት ከመንቀሳቀስ ባሻገር የትምክህት አስተሳሰብ የተጠናወተው አስተሳሰብና ተግባር ጐልቶ ወጥቷል። ጉዳዩ በሁለት ወረዳዎች መካከል በጥቂት አዋሳኝ ስፍራዎች ላይ ያለ ሆኖ ሳለ፣ ከደረጃውና ከጉዳዩ ልክ በላይ ተጋኖ እንዲታይ አድርጓል።
የቅማንት ብሔረሰብ የማንነትና የራስ አስተዳደር ጥያቄን በወቅቱ አይቶ በዴሞክራሲያዊ አግባብ መፍታት ሲገባው፣ የትምክህት አስተሳሰብና ተግባር በመበራከቱ ምክንያት በወቅቱ ሳይፈታ ከመቅረቱም በላይ ብዙ ጉዳት ደርሷል። ከወልቃይት ህዝብ ማንነት ጋር ተያይዞ በተነሳው ውዝግብም አመራሮችና አባላት ቀጥታ በማያገባቸው ጉዳይ ገብተው ህዝብን ለጉዳት የዳረጉበት እንደሆነ በግምገማ ተረጋግጧል። በወልቃይት ማንነት ዙሪያ ባለቤቶቹ ከቦታው እያሉና ጥያቄ ካላቸው በራሳቸው ታግለው መብታቸውን ሊያስከብሩ እየቻሉ፣ የሌሎች አጀንዳ በሆነ ጉዳይ ተስቦ በመውጣት ወይንም ቀጥተኛ አግባብ በሌለው ጉዳይ ውስጥ ገብቶ አካባቢን የሚያተራምስ መጥፎ ውድቀት ውስጥ እንደገባ በግምገማችን ተረጋግጧል።
አመራሮችም ሆኑ አባላት በተዛባ መረጃ ላይ ተመስርተው እህት ድርጅቱን ተጠራጥረዋል። የአፈፃፀም ችግሮችን በማንሳት ዴሞክራሲያዊና ፀረ-ዴሞክራሲያዊ ኃይሎችን ቀላቅለው ተመልክተዋቸዋል። የትምክህት ኃይሉ አመራሩን ለመከፋፈል ሲንቀሳቀስ የጠላትን አስተሳሰብ ተሸክሞ አራግቧል። ተደራጅቶ መመከትና መታገል ሲገባው፣ አይቶ እንዳላየ በተደራዳሪነት ተመልክቷል። ከሁሉም ብሔሮች የተነሱ ጥገኞችን በኩል መዋጋት ሲገባው “የእኛና የእኛ ያልሆነ” በሚል ሸፍኖ የመሄድ አስተሳሰብ፣ የአመራሩ ትምክህተኛ አመለካከትና ተግባር አንድ ማሳያ ሆኖ ታይቷል። የራሱን ብሔር ጥገኞች የቅድሚያ ትኩረት ሰጥቶ በሚፈለገው ደረጃ አልታገለም። በህዝባችን መካከል ዴሞክራሲያዊ አንድነት እንዲጠናከር የሰራው ስራ ደካማ ነው። ብዝሃነትን የማይቀበሉና የዴሞክራሲያዊ አንድነት እንቅፋት የሆኑ አስተሳሰቦችንና ተግባራትን በብቃት አልታገላቸውም። የአክራሪነትና የጠባብነት አመለካከቶችና ተግባራት፣ ከባቢያዊነትና ጎጠኝነት በተለያዩ ደረጃዎች የሚስተዋሉ ሲሆን፣ እነዚህን ችግሮች የታገለበት አግባብም ወጥነት አልነበረውም።
በየተቋሞቹ የትምክህት አስተሳሰቡ በስፋት ገኖ ሲወጣ፣ ከፍተኛ አመራሩ በራሱ የሚታየው እንደተጠበቀ ሆኖ፣ የመታገልና የማስተካከል ሁኔታው ከአመራር በሚጠበቅ ቁመና አልነበረም። አክራሪነትን አጥብቆ በመታገልና ከመሰረቱ አስተሳሰቡንና ተግባሩን ለማጥፋት ወጥና ጠንካራ እንቅስቃሴዎችን አላካሄደም። ትምክህት በአስተሳሰብም፣ በተግባርም ጣራ ነክቶ ችግር እየፈጠረ በነበረበት ወቅት አዲስ ነገር እንዳልተፈጠረ አድርጐ አቅልሎ የማየት ችግር ታይቶበታል። እነዚህ ችግሮች ተዳምረው ክልላዊና አገራዊ ህዝባዊ አንድነታችንን የጎዱ አደገኛ አዝማሚያዎች በመሆናቸው ለቀጣይ ትምህርት በሚሆን አግባብ መታረም አለባቸው።
የነዚህ ሁሉ ችግሮች መነሻ ምንጮችና መንስኤዎች
አመራሩ የያዘውን ህዝባዊ ኃላፊነት የህዝብ ኑሮ መለወጫ ማድረጉ ቀርቶ የስልጣን አተያዩና አጠቃቀሙ የተዛባ ሆኖ እንደሰነበተ በግምገማ ተለይቷል። አመራሩ ኃላፊነቱን የኑሮና አልፎ አልፎ የሀብት ምንጭ መሰረት አድርጎ የመጠቀም በአስተሳሰብና በተግባር የመውሰድ ዝንባሌ ተስተውሎበታል። ይህ ደግሞ ከህዝባዊ ወገንተኝነት መራቅና ከዓላማ ጽናት መጓደል ጋር የተያያዘ ችግር ሆኖ ተገኝቷል፤ በመሆኑም በተሀድሶ ንቅናቄ የተለዩትን ችግሮችና የችግሮቹን መንስኤዎች በብቃትና በኃላፊነት መንፈስ ተረድቶ ለውጥ ለማምጣት ቀጣይ ርብርብ ማድረግን ይጠይቃል።¾