ኢትዮጵያዊው ማን ነው? ፤ ኢትዮጵያዊነት ምንድን ነው?
እጅግ ይገርማል ይደንቃል ፤ ኢትዮጵያዊነት ምን እንደሆነ
ኢትዮጵያዊውም ማን እንደሆን ፤ አጠራጥሮ ደመነ?
የኢትዮጵያዊው ኢትዮጵያዊነት ፤ ማንነቱና ምንነቱ
ደብዝዞ እስኪያምታታ ፤ አስቸገረ መለየቱ ?
ለዚህም ተዳርሰናላ ፤ ጭራሽ ጥያቄ እስኪያስነሣ?
መሬት ሲያረጅ ምን ያበቅላል ፤ ይሉት ደርሷላ አበሳ
ኢትዮጵያዊው ማን ነው? ፤ ኢትዮጵያዊነት ምንድን ነው?
ኢትዮጵያዊነት ሲጎዳ ፤ ሲሸረሸር በነፋስ ሲታይ
ሲገፈተር ሲሽቀነጠር ፤ ሲወድቅ አደጋ ላይ
የተፈጠረ ጥያቄ ፤ የሀገር ፍቅርን አግላይ
ሀገር በቀል እሴቶችን ፤ ያለርሕራሄ ገዳይ
የተማረከ የተበነደ ፤ የሚያነሣው ሲሆን አባይ
ኢትዮጵያዊነትን ያስረጀ ፤ ክህደትን ያሠለጠነ
የተሠወረ ይመስል ፤ ድብቅ ምሥጢር የሆነ
የሐበሻነትን መለያ ፤ በአደባባይ ያኮሰመነ
የእንቢተኝነቱን ጽናት ፤ ከውስጥ ሰልቦ ያመነመነ
ብቁ ትጉ ዜጎቿን ፤ ጆሮ አስይዞ ያስመነነ
የቃል ኪዳን ልጅነትን ፤ እያስካደ ያስኮነነ
ታሪክ ቅርስ እሴታችንን ፤ ከል አልብሶ የከደነ
ሐሰት ሐሰቱን ያነገሠ ፤ እውነት እውነቱን ያዳፈነ
የራስን ወርቅ አስጥሎ ፤ መዳብ ጠጠር ያስለመነ
ሕዝብን የናቀ ያሳዘነ ፤የተዳፈረ ሉዓላዊነት
ወገናዊ ያልሆነ ፤ ባዕዳዊ ሸፍጥ ምጸት
በሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ ፤ የተደበቀ እብለት
እውነቱ እየታወቀ ፤ በገሐድ በፋኖ ሕይዎት
የሀገራቸውን ጥቅሞች ፤ ለድርድር በማያቀርቡት
ለሉዓላዊነት ሲሉ ፤ ሞትን ገለው በሚሞቱት
ኢትዮጵያዊውን እሴት ፤ በጽናት በሚጠብቁት
በቀደመው በጥንት ዘመን ፤ ከሀገር አልፎ በአህጉራት
ኢትዮጵያዊነት በምልዓት ፤ ናኝቶ በነበረበት
በዚያ ዘመን ቢነሣ ፤ ሆኖ የሚታይ እብደት፡፡
በል እንግዲህ ወገኔ ፤ አውቀህም ይሁን ሳታውቅ
ጠይቀሀልና ጥያቄ ፤ በእጅጉ የሚያስደንቅ
ኢትዮጵያዊነት ማለት ፤ ሲተነተን ሲዘረዘር
ከአደኛኘት እስከ አሞጋገት ፤ ከአስተዛዘን እስከ አመራረር
ከአስተካከም እስከ አገነባብ ፤ ከአሣሣል እስከ አነጣጠር (አንጠረኛ)
ከአጠናን እስከ አፈለሳሰፍ ፤ ከአነባበብ እስከ አመሠጣጠር
ከአወጋግ እስከ አመራረክ ፤ ከአቀራረብ እስከ አመራመር
ከአጻጻፍ እስከ አቆጣጠር ፤ ከአስተሳሰብ እስከ አኗኗር
ከአከዋወን እስከ አቀጣጠር ፤ ከአዘገጃጀት እስከ አከባበር
ከአመጋገብ እስከ አለባበስ ፤ ከአስተዳደግ እስከ አነጋገር
ከአፈነጣጠዝ እስከ አለቃቀስ ፤ ከአዚያዚያም እስከ አደነካከር
ከአመራረቅ እስከ አረጋገም ፤ ከአመላለክ እስከ አሥተዳደር
ለዓለም የተገለጠ ፤ በመልከጼዴቅ በዮቶር
የራሱ መሠረት ያለው ፤ የሥልጣኔ ፈለግ
የራሱ ትውፊት ያለው ፤ እውነት የሆነ የሚታደግ
የራሱ ቀለም ያለው ፤ የብቻው መለያ ብልጹግ
የራሱ እምነት ያለው ፤ የተለየ ባሕልና ወግ
የራሱ ሥርዓት ያለው ፤ አከዋወን አደራረግ
የራሱ ይትበሀል ያለው ፤ የተወደዱ ደጋግ
ምዕራባዊ ያልሆነ ፤ ምሥራቃዊም ወዲያ ጥግ
ዓረባዊ ያልሆነ ፤ አውሮፓዊም አጭሉግ
ከማንም ያልተወረሰ ፤ ያልመጣ ተሻግሮ አፍላግ
ያወረሰ እንጅ የሰጠ ፤ ሁሉን ያረገ ዕዱግ
የራሱ ብቻ የሆነ ፤ ሉዓላዊ ማዕረግ
ይሄ ማለት ነው ወዳጀ ፤ የኢትዮጵያዊነት ድር ማግ
ይሄንንም የሚኖረው ነው ፤ ኢትዮጵያዊው ብትፈልግ፡፡
ወደ ኋላህ ተመልሰህ ፤ ማንነትህን ብትፈትሽ
ቱባውን ታገኘዋለህ ፤ ሳይበራረዝ ሳይበላሽ
ሲጠበቅላት የኖረውን ፤ በንግሥታት ነገሥታቷ
ከራሷው የበቀለውን ፤ የሆነውን የገዛ ሀብቷ
ኢትዮጵያዊ መሆን ካሻህ ፤ ጽዱ ንጥር ሐበሻ
አምጣውና ያንን ኑረው ፤ መደበላለቅ ሳትሻ
ያንን ተቀባ ተላበሰው ፤ አውልቀህ የሌላን ቆሻሻ
ዱካህ ብቻ ነው መድኅንህ ፤ ከጥፋት ማምለጫ መሸሻ
በልክህ የተሠራልህ ፤ አይጠብ አይሰፋህ ድርሻ
ይሄንን ሳታደርግ ግን ፤ ሳትመለስና ሳትረዳ
ኢትዮጵያዊ ነኝ እንዳትል ፤ እሷ አታውቅህም ነህ ባዳ
ምሁር ዐዋቂ ነኝ እንዳትል ፤ ጎሎሀል ዕውቀት የላቀ
ራስን የማወቅ ያህል ፤ አክብረህ መመስከር ላላወቀ
ጤነኛም ነኝ እንዳትል ፤ ይዞሀል የአእምሮ በሽታ
አንተነትህን አስጠፍቶህ ፤ ሌላ እንድትሆን የሚያምታታ
ይሄን በሚያህል ድንቁርና ፤ ወርቅ አንተነትህን ባስናቀ
ተውጠህ ሰምጠሀል ውጣ ፤ ዕውቀት አለልህ የመጠቀ
ይሄን በሚያህል በሽታ ፤ ሉዓላዊ ክብርህን ባስጣለ
ተለክፈህ አብደሀል ንቃ ፤ ጤና አለልህ ያማለለ
ድንቁርናው በርትቶብህ ፤ የለኝም ካልከኝ በር መውጫ
በሽታውም ጸንቶብህ ፤ አጣሁ ካልከኝ ፈውስ መስጫ
ከቶውንም ቃናው የለህ ፤ የኢትዮጵያዊነት መገለጫ
ምንም እንደሆንክ አላውቅም ፤ ለምን ምንድን ነው ያንተ ምርጫ ?
ነጭ ነው ቢጫ ወይስ ዓረብ ፤ መልክህ ምንድን ነው ዓይነቱ ?
የማንነትህ ምንጭ አሻራ ፤ ወዴት ይመስልሀል መሠረቱ ?
አይደለም እንዳትሳሳት ፤ ያለህን አሳይ ሐቅ አውራ
እራስህን አታጃጅል ፤ ጆሮህን አትስጥ ለፈጠራ
የነጭ ቢጫ ዓረብ አይደለም ፤ ነው እንጅ የጥቁር አውራ
የተገፋው ሕዝብ መመኪያ ፤ መኩሪያ መከታ ባለአደራ
እራስህን ጠይቅ መርምረው ፤ ታሪክን አስመስክር ለእምነቱ
ልማዳዊ አይሁን መንገድህ ፤ ውስጥህ ምን ይልሀል ስሜቱ?
ራስህን ለእውነት አስገዛ ፤ ምክንያታዊ ይሁን ስሌቱ!
ወገናዊ ይሁን አድልኦህ ፤ ኢትዮጵያዊ ይሁን ቅኝቱ!
እራስህን ቅጥረኛ አርገህ ፤ የጠላት ሎሌ አትሁን ከንቱ!
ጠፍተህ ለማጥፋት አትትጋ ፤ ይሰማህ የክህደት ውርደቱ!
የማንም ምስክር አያሻህ ፤ ሕሊናህ ውስጥ አለ እውነቱ!
ከራስህ ተለይተህ ላትለይ ፤ ሆነህ ላትሆን ሌላ
ምንም አማራጭ የለህም ፤ ድመቅ በራስህ ገላ!
ተመለስ ከክህደትህ ፤ ሆነህ እንዳትቀር ሰንካላ!
አቅመቢስ ድኩም ሰባራ ፤ ለምንም የማይሆን ሰላላ!
ንቃ ከመተተኞች ፍዘትህ ፤ አዚሙን ሽረህ በኤላ
ተመለስ ወደአንተነህ ፤ እሱ ነው የሚያዋጣህ ከለላ፡፡
ሥራ በእናት አባትህ ትጋት ፤ በሰጠን ኃያሉን ዱላ!
ቀድሞ አንግሦህ በነበረው ፤ እስከ እስያ ሁላ!
ትጋ ተሯሯጥ ጽና ፤ ቅበር ስንፍናን ጥላ!
አሳድ ድህነትህን አባር ፤ አርቅ ከሀገርህም ክላ!
ባርክ በአንተው ጸሎት ፤ መርቅ ሕይዎት ለአንተ ታዳላ!
ፈትን በራስህ ጉልበት ፤ ዘይድ በራስህ መላ!
ኩራ በአንተው ማንነት ፤ ዝመት ወኔህን ሙላ!
ፎክር በአንተው ጋሻ ጦር ፤ ደንፋ በአንተው ሽለላ!
አቅራራ በአንተው ቀረርቶ ፤ ብረቅ እንደ እሳት ጎመራም ፍላ!
አውጅ ነጋሪት ጎስም ፤ ጨክን በሠይፍህ ቅላ!
ምጠቅ በራስህ ዕውቀት ፤ ጽና በራስህ መሐላ!
አውጋ በራስህ ቋንቋ ፤ ተቀኝ ቅኔህ ይራቀቅ ይስላ!
ፍረድ በራስህ ፍትሕ ፤ በዳይ እንዳይኖር ሚያጉላላ!
አንብብ በራስህ ፊደል ፤ ቀምር በቁጥርህ አስላ!
ብራና መጻሕፍትህን ፤ ሲሳይ ያወረዱትን ለሌላ!
እያንዳንዳቸውንም በዝብዝ ፤ ጥርግርግ አርግና ብላ!
አዚም በራስህ ዜማ ፤ አስንቅ ሌላን አስጠላ!
አዝምር በራስህ ሁዳድ ፤ መጽውት መዓድህን ሙላ!
አክብር የራስህን በዓላት ፤ መንፈስህ ይታደስ በተድላ!
ሙሉ ነውና ማንነትህ ፤ በራስህ እሴቶች ጉላ!
ከማንም ምንም አያሻህ ፤ ዕወቅ አትሁን ተላላ!
እንኳን ለራስህ ቀርቶ ፤ ብዙ ተርፈሀል ለሌላ፡፡
ኢትዮጵያዊና ኢትዮጵያዊነት ፤ በእነዚህ እሴቶች ካልተለካ
በምን ይመዘን ይመስልሀል ፤ ሀገርስ በምኗ የምትመካ ?
ከአማራ ኦሮሞ ትግሬ ፤ ከጉራጌ ወላይታ ሱማሌ
ከሁሉም ብሔረሰቦች ፤ እነዚህን እሴቶች ካለ አሌ
ኢትዮጵያዊነት ውስጡ የለም ፤ ሸጦ በልቶታል በአሞሌ!
ይማር ይመከር ይገራ ፤ እራሱን እስኪያውቅ ተላሌ፡፡
ብቻ የራሳችን ይሁን እንጅ ፤ የተገነባ በሐበሻ ዘየ
የአማራ እሴት ነው የተባለው ፤ የሱማሌውም ሆኖ ካልታየ
የወላይታው ሀብት የተባለው ፤ የትግሬውም መሆኑ ከታበለ
እሱ ደሞ እዚህ ምን አገባው ፤ የኔ ጉዳይ ነው ከተባለ
ይሄ ሰው ምኑም አልገባው ፤ ገና ገና ብዙ ችግር አለ፡፡
በል እስኪ ንገረኝ እኮ በል ፤ ኧረ እንዴት ሆኖ ነው ወገኔ
ሁላችንም እንዲህ እያልን ፤ ያሰብን ጊዜ ያኔ
አንድነት ያለው ጠንካራ ሕዝብ ፤ ያልተቃረጠ ሥልጣኔ
ሰላማዊት ምቹ ሀገር ፤ ሉዓላዊ ማንነት ውርስ
ዘመን ተሸጋሪ ታሪክ ፤ ሳይበረዝ ሳይከለስ
እንደምን ሆኖ ይኖርሀል ፤ መቸና ከወዴት ሊመጣ?
ምንስ ያሰመጠህ መሰለህ ፤ እዚህ ካለህበት ሁሉ ጣጣ?
መውደቅ የጀመርክበትን ዘመን ፤ መለስ ብለህ ብታየው
ሌላም ምክንያት አልነበር ፤ እንደዚህ ባሰብክ ጊዜ ነው፡፡
የኔ ነው ሌላው ምን አገባው? ፤ የምትለው ቅርስ የተጫነ
ተው ሲታወቅብህ ታፍራለህ ፤ ያ ቅርስ የአንተ እንዳልሆነ!
ነገሮች ተገለባብጠው ፤ የታሪክ አጋጣሚ ሆነና
የአንተ እንደሆነ እንድታወራ ፤ አረገህ ጊዜ ሳተና
ባለቤቱ ዝም ያለውን ፤ የሁሉም ነው ብሎ አስቦ
አንተም እያወክ እውነቱን ፤ ልትነጥቅ ከዳዳህ ከደቦ
እውነቱ ይነገርሀል ፤ ዋ ትዋረዳለህ በኋላ!
ዐርፈህ ተቀመጥ በአደብ ፤ በእናት ኢትዮጵያ እንዳትጠላ፡፡
ወገኔ እኔስ ልመርቅህ ፤ ነው ብለህ እንዳትንቀው የኩታራ
ልብ ይስጥህና ያድርግህ ፤ በማንነትህ የምትኮራ!
በፍቅር በመከባበር ፤ ተሳስበህ ጠባቂ አደራ!
የማይፈታ አንድነት ያለህ ፤ በእኩያን ጠላቶች ሴራ!
የማንነት እሴቶችህን ፤ በሉላዊነት ሽርሸራ
ለድርድር ያማታቀርብ ፤ ቆራጥ ሀሞተ ኮስታራ!
በራስህ ዱካ እሮጠህ ፤ ሌሎቹን ባረገው ሲራራ
ለስኬቶችህ የምትበቃ ፤ በመላው ዓለም የምትበራ!
የምትደምቅ የምትፈካ ፤ የምትነግሥ የምትፈራ!
አሜን! በለኛ ወገኔ ፤ ልሳንህ አሜንን ይጣራ!
ከአሜን ይቀራልና ፤ አሜን አሜን አሜን ምራ!
አሜን አሜን አሜን ምራ ፤ አሜን አሜን አሜን ምራ!
ጥቅምት 2004 ዓ.ም.
ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው
amsalugkidan@gmail.com