ባይሳ ዋቅ –ወያ (ጄኔቫ)
ሰኔ 30 ቀን 2017 ዓ/ም
ለዚህ ጽሁፌ መነሻ የሆነኝ ባላፈው ሳምንት የኢትዮጵያ መንግሥት ባገሪቷ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 49(5) የተደነገገውን አስመልክቶ የኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ ላይ ያላትን ልዩ ጥቅም ለማስጠበቅ ብሎ ያወጣው ረቂቅ ዓዋጅ ነው። በኔ ግምት የዓዋጁ ከሁለት ዓስርተ ዓመት መዘግየት በኋላም ቢሆን ዛሬ ይፋ መውጣቱ አዎንታዊ ገጽታ ያለው ቢመስልም መንግሥት በቀና መንፈስ ያደረገው ሳይሆን ባገሪቷ ውስጥ በተከሰተውና በመከሰት ላይ ባለው የፖሊቲካ ቀውስ ተወጥሮ ያደረገው ይመስለኛል። ከዚያም በላይ ዓዋጁ የተደነገገው በሕገ መንግሥቱ ለኦሮሚያ ክልል ቃል የተገባለትን ጥቅም ለማስጠበቅና የታለመለትን ግብ ለመምታት ሳይሆን የኦሮምያን ክልል ለይቶ የጠቀመ እያስመሰለ በሕዝቦች መካከል መጠራጠርንና ብሎም መከፋፈልን ለማንሰራፋት የተወጠነ በማር የተለወሰ መርዝ ነው ብዬ ብል ከእውነት ያልራቅሁ መሆኔን እርግጠኛ ነኝ። አባባሌን በተጨባጭ ማስረጃ ለማስደገፍ እስቲ የረቂቅ ዓዋጁን ይዘት በጥልቁ እንመርምር። ከዚያ በፊት ግን እንደሁ በቅንፍ ውስጥ ዝቅ ብዬ ለማቀርባቸው አስተያየቶች መሰረት ይሆናሉ ብዬ የማስባቸውን ጥያቄዎች ለማቅረብ እሻለሁ።
ያኔ ሕገ መንግሥቱ ሲደነገግ ”የኦሮሚያ ልዩ ጥቅም“ የተባለው ዓረፍተ ነገር ሲታከልበት በኦሮሚያ ክልልና በፊንፊኔ መካከል ያለው ሕጋዊ ግንኙነት በጥልቅ ውይይት ተደርጎበት ስምምነት ላይ ተደርሶ ነበር ወይ? ከሆነስ ያኔ የተደረሰበት ድምዳሜ ፊንፊኔ የኦሮሚያ ከልል ናት ወይስ ራሷን የቻለች ልዩ ግዛት ነበር የሚለው? ለኦሮሚያ ክልል “ልዩ ጥቅም” የተባለው፤ ፊንፊኔ “በኦሮሚያ ክልል መሃል የምትገኝ” እና በኦሮሚያ ክልል ስለተከበበች ተብሎ ነው ወይስ “የኦሮሚያ ከልል አካል ስለሆነች”? ሕገ መንግሥቱስ ሲደነገግ በኦሮሚያ ክልል ባለሥልጣናትና በፌደራል መንግሥቱ መካከል ግልጽ የሆነና ጣምራ ትርጉም የሌለው አቋም ተወስዶ ነበር ወይ? እነዚህን ጥያቄዎች ያነሳሁት ያለ ምክንያት አይደለም። ረቂቅ ዓዋጁን አስመልክቶ አሁን በኢትዮጵያውያን መካከል በመካሄድ ላይ ያለው ውይይት አይሉት መናቆር፤ ሁለት ዱዳና ደንቆሮ የሆኑ ግለሰቦች የሚያወሩትን ያህል በምንም ተዓምር መግባባት ሊደረስበት የማይቻልበት ሁኔታ ላይ የደረስን ስለመሰለኝ ነው።
የረቂቅ ዓዋጁ ይዘት፤
ረቂቅ ዓዋጁ ገና ከመጀመርያው በአንቀጽ 2 (4) በግልጽ ያስቀመጠው የአዲስ አበባን “በኦሮሚያ ክልል መሃል” መገኘት ነው። ይህ እንግዲህ እያንዳንዱ አንባቢ እንደፈለገው እንዲተረጉመው ተብሎ መሰለኝ። ኦሮሞዎች ፊንፊኔ የኦሮሚያ አካል ናት ሲሉ መንግሥት ደግሞ፤ አይ አይደለም፤ ፊንፊኔ በኦሮሚያ ክልል መሃል የምትገኝ ማለትም በኦሮሚያ ክልል የተከበበች እንጂ የኦሮሚያ ክልል አካል አይደለችም የሚል መሰለኝ። ዓዋጁ “የኦሮሚያን ክልልን ልዩ ጥቅም ለመወሰን” የወጣ ነው ይልና ይጠበቃሉ የተባሉትን “ልዩ ጥቅሞች” ሲደረድር የትምህርት የጤና የባህል ቋንቋና ሥነጥበብ አገልግሎቶች በማለት፤ ይጠቅሳል። በኢሕአዴግ አባባል የተዘረዘሩቱ “ልዩ ጥቅሞች” የተሰጡት የኦሮሚያ ክልል ፊንፊኔ ላይ ባለው ሕጋዊ መብት ላይ ተመሥርቶ ሳይሆን መንግሥት በበጎ ፈቃዱ ለክልሉ የቸረው ነው ማለት ነው። ከሕግ ትርጓሜ አንጻር ካየነው ግን እነዚህ የተወሱት ”ልዩ ጥቅሞች“ ፊንፊኔ ከተማ ውስጥ የሚኖር ማንኛውም ዜጋ በእኩልነት ሊያገኛቸው የሚገባ የሰው ልጆች መብት እንጂ መንግሥት ለይቶ ፊንፊኔ ውስጥ ለሚኖሩ የኦሮሞ ብሄር ተወላጆች ብቻ የሚሰጥ የችሮታ ዕቃ አይደሉም። እንደሁ መንግሥት በማን አለብኝነት ወይም ”በኃዜኔታ“ ከፊንፊኔ ነዋሪዎች መሃል ለይቶ ሃያ በመቶ የሆኑትን ኦሮሞዎችን ብቻ ልዩ ተጠቃሚ አደርጋቸዋለሁ ካለ ደግሞ፤ ድርጊቱ እውነትም ልዩ ጥቅም ወይም ፈረንጆች እንደሚሉት (preferential treatment) ነው እንጂ የመብት ጉዳይ አይደለም ማለት ነው። “ልዩ መብት” እስካልሆነ ድረስ ደግሞ በፊንፊኔ የሚኖሩ ኦሮሞች እንደማንኛውም የከተማው ነዋሪዎች፤ ለምሳሌ እንደ ሕንድ፤ የአርመን እና የጀርመን ኮሙኒቲ የኦሮምኛ ትምህርት ቤት፤ ፊልም ቤት፤ ቤተ መዘክር ወይም ቴያትር ቤት ከፍተው እኩል ሊደሰቱ ይችላሉ ማለት ነው። ለዚህ ደግሞ “ልዩ ጥቅምን” የሚደነግግ የተለየ ዓዋጅ አያስፈልግም።
መደረግ ያለበት፤
በመጀመርያ ደረጃ አሁን በመካሄድ ላይ ላለው አለመግባባት መንስዔው በሕገ መንግሥቱ ውስጥ የተካተተው አንቀጽ 49(5) ግልጽ ሆኖ ያለመቀመጡ ጉዳይ በመሆኑ መንግሥት ከሚመለከታቸው የፌዴራልና የኦሮሚያ ክልል መንግሥት አካላት ጋር በመሆን የማያወላውልና ቀጥተኛ ትርጉም ባለው አንቀጽ እንዲተካ መደረግ አለበት። ኦሮሞዎች፤ ያኔም አሁንም የሚፈልጉት ፊንፊኔ የኦሮሞዎች ርስት መሆኑ ታውቆ ሕጋዊ ባለቤትነታቸው እንዲረጋግጥላቸው ስለሆነ ይህ የባለቤትነት መብታቸው በሚስተካከለው አዲስ የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 49(5) በግልጽ መቀመጥ አለበት። ይህ በመጀመርያ ደረጃ መመለስ ያለበት ቁልፍ የሆነ የባለቤትነት ጥያቄ ነው። ለዚህ ቁልፍ ጥያቄ መልስ ከተገኘ ደግሞ የተቀረው ሁሉ በቀላሉ ዕልባት ያገኛል። አለበለዚያ ግን የፌዴራል መንግሥቱ ያለሕጋዊ ባለቤቶቹ በጎ ፈቃድና ስምምነት ሕገ መንግሥታዊ ባልሆነ መንገድ የከተመበትን መሬት ራሱን እንደ ሕጋዊ ባለቤት ቆጥሮ የልዩ ጥቅሞች “ሰጪ” በመሆን የመሬቱን ሕጋዊ ባለቤቶችን ማለትም ኦሮሞዎችን ደግሞ “ተቀባይ” ለማድረግ መሞከር የሌባ ዓይነ ደረቅ እንደሚሉት ዓይነት ከመሆን የተለየ ትርጉም አይኖረውም።
ክልሎች ሁሉ በየራሳቸው ምርጫ በክልላቸው ውስጥ ከሚገኙት ከተሞች መርጠው የየራሳቸውን ዋና ከተሞች መሥርተዋል፤ የኦሮሚያ አስተዳደርም በክልሉ ውስጥ ከሚገኙት ከተሞች ሁሉ ፊንፊኔን መርጦ ዋና ከተማው አርጎት ባገሪቷም ሕገ መንግሥት አስጸድቆታል። የፈዴራል መንግሥቱ ደግሞ ባገሪቷ ውስጥ ከክልሎች አስተዳደር ነጻ የሆነ በፈዴራሉ መንግሥት የሚተዳደር ትርፍ መሬት ባለመኖሩ በተለምዶ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ተብላ የታወቀችውን አዲስ አበባን ያለምንም ቅድመ ድርድር ዋና መቀመጫው አርጎታል። እንደ ፌደራል መንግሥት መቀመጫውን ቢፈልግ ሃዋሳ ወይም ሁመራ ወይም ጂማ ማረግ ይችል ነበር። ግን አስፈላጊ አልነበረም። ለወደፊትም ደግሞ አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ አዲስ አበባን የንግድ መናሀርያ አርጎ የኢትዮጵያን ዋና ከተማ፤ ለምሳሌ የናይጄሪያና የፓኪስታን መንግሥታት እንዳደረጉት፤ አመቺ ወደሆነ ሌላ ከተማ ወይም ቦታ ሊያዞር ይችላል። ይህ ደግሞ ጉዳዩ በሚመመለከታቸው የክልሉ አስተዳዳሪዎች መልካም ፈቃድና ውሳኔ ላይ የተመሰረተ መሆን አለበት።
ወደድንም ጠላንም ዛሬ ያለው የኢትዮጵያ አስተዳደራዊ መዋቅር ፌዴራላዊ ነው። የድኅረ ወያኔ ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ የግዛትና አስተዳደር ሁኔታ ደግሞ በሕዝቦቿ እኩል ተሳትፎና ፈቃድ የሚወሰን ስለሆነ ዛሬ ግምታዊ የሆነ እሰጥ አገባ መጀመር ያለብን አይመስለኝም። እስከዚያው ድረስ ግን ኦሮሚያ ክልል እንደሆነች ትቀራለች፤ ፊንፊኔም የኦሮሚያ አካል እንደሆነች ትቀጥላለች ማለት ነው። ፊንፊኔ የኦሮሚያ ክልል አካል ሆነች ማለት ግን በኗሪዎቿ ላይ አንዳችም የግለሰብም ሆነ የቡድን የመብት ጥሰት አያስከትልም። የተለያዩ ብሄረ ሰብ አባላት ቋንቋቸውንና ባህላቸውን ያለምንም ተጽንኦና አድልዖ የማሳደግና የማስፋፋት መብታቸው ይጠበቃል ማለት ነው፤ ዜጎች በሕጉ መሰረት የሚወሰንባቸውን ግብር ይከፍላሉ፤ በሙያቸው ከማንኛውም ዜጋ እኩል ያለምንም መድልዖ ሥራ ያገኛሉ፤ ፊንፊኔ ማንም ከማንም የተለየ ወይም የተሻለ “ልዩ ጥቅም” የማያገኝባትና ሁሉንም እኩል የምታስተናግድ የኦሮሚያም የኢትዮጵያም ዋና ከተማ ሆና ትቀጥላለች ማለት ነው።
ዛሬ በአስቸኳይ መፈፀም ያለበት አንድ ዓብይ ጉዳይ አለ። የፊንፊኔ ከተማ ወሰን በአግባቡ ሳይከለል በልማት ሰበብ በመስፋፋቷ በዙሪያዋ ለሚኖሩት ብዙ ኦሮሞዎች ከመሬታቸው መፈናቀልና ለድኅነት መዳረግ ምክንያት በመሆኑ የከተማው ድንበር በግልጽና በማያሻማ መንገድ በአስቸኳይ መከለል አለበት። ከተማው ከድንበሩ ውጭ ተፈጥሮአዊ ዕድገትን ተከትሎ ወደ ኦሮሚያ ክልል በሰፋ ቁጥር ላስከትለው የሕዝቦች መፈናቀልም ተገቢው ካሳ መክፈል ብቻ ሳይሆን ወደፊትም እንዳይደገም መንግሥት ዛሬውኑ የማያወላውል እርምጃ መወሰድ አለበት። የፊንፊኔን ወደቀሪው የኦሮሚያ ክፍል መስፋፋት ማንም ሊያቆመው የማይችል የከተሞች ዕድገት ተፈጥሮአዊ ክስተት ነው። ሕጋዊና ተፈጥሮአዊ የማይሆነው ግን በልማት ሰበብ የዜጎች መሠረታዊ የሰው ልጆች መብት ሲደፈር ነው።
በመጨረሻ ለማሳሰብ የምወደው ግን፤
ሀ) ፊንፊኔ የኦሮሚያ ክልልና አካል ነች ማለት ሕጋዊ ባለቤትነትን ለማጽደቅ ታስቦ እንጂ ዛሬ የከተማዋ ነዋሪ በሆኑት የተለያዩ ብሄርና ብሄረሰቦች ላይ አንዳችም የጊዜያዊም ሆነ ቋሚ የአኗኗር ወይም የአሰራር ለውጥ ለማስከተል አይደለም። አንድ ብቸኛ ለውጥ ቢኖር የከተማዋ አስተዳደር በፌዴራል መንግሥት መሆኑ ቀርቶ በኦሮሚያ ክልል ሥር ይሆናል ማለት ነው። ይህ ደግሞ በኗሪው ሕዝብ ሥራና ሕይወት ላይ አንዳችም ለውጥ አያወጣም። የፊንፊኔም ኗሪ ሕዝብ ማንነትም (demography) በሰው ሠራሽ ውሳኔ ሳይዛባ የተፈጥሮ ሂደትና ዕድገት ተከትሎ ጉዞውን ይቀጥላል ማለት ነው።
ለ) ኢሕአዴግ ዛሬ ሕገ መንግሥቱ ከጸደቀ ከሃያ ዓመት በኋላ ይህንን “ልዩ ጥቅም” የሚለውን ሸፋፋ ሰበብ ከተቆለፈበት መጋዘን አውጥቶ ለኦሮሞ ሕዝብ የተቆረቆረ አስመስሎ ለገበያ ማቅረብ፤ እውነትም የተዛባውን ፍትህና የአላግባብ ባለቤትነትን ዘረፋ ለማስተካከል ብሎ ሳይሆን “ጭር ሲል አልወድም” እንዳለችዋ ዘፋኝ እህታችን ሕዝቡን ለማመስና ብሎም እርስ በርስ ለማጋጨት ታስቦ ስለሆነ፤ የኢትዮጵያ ሕዝቦች በተለይም በዲያስፖራ ያሉት ዜጎች ይህንኑ በቅጡ አስተውለው ካላስፈላጊ የጥላቻ ውይይትና አመለካከት እንዲቆጠቡ አደራ እላለሁ። አመሰግናለሁ።
*******
ባይሳ ዋቅ –ወያ
(ጄኔቫ)
ሰኔ 30 ቀን 2017 ዓ/ም